ባህላዊ ሙዚቃዎች ለአማራ ህዝብ በደል ፍትህና አንድነት ያላቸው ሚና፣ በ2013ዓ.ም በወጡ የአማርኛ የባህል ሙዚቃ ግጥሞች ማሳያነት
DOI:
https://doi.org/10.20372/ajcik.2023.2.1.933Abstract
የዚህ ጥናት ዋና ዓላማ ባህላዊ ሙዚቃዎች ለአማራ ህዝብ በደል ፍትህ፣ አንድነትና ልማት ያላቸውን ሚና ማሳየት ነው፡፡ ጥናቱ አይነታዊ የምርምር ዘዴን በመጠቀም በይዘት ትንተና ስልት ተካሂዷል፡፡ ለጥናቱ አገልግሎት ላይ የዋሉ የአማርኛ ባህላዊ ሙዚቃዎች የተሰበሰቡት ከዩትዩብ ማህበራዊ ሚዲያ ነው፡፡ በዩትዩብ ማህበራዊ ሚዲያ በበርካታ ቋንቋዎች ኢትዮጵያውያን ያዜሟቸው ወቅቱን የዋጁ ዘፈኖች አሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ለጥናቱ በአማርኛ ቋንቋ ተሰርተው ወቅታዊ የሀገሪቱን ሁኔታ የሚመለከት ይዘት ያላቸው ባህላዊ ሙዚቃዎች ብቻ በዓላማ ተኮር የንሞና ዘዴ ተመርጠዋል፡፡ በዚህም መሠረት 18 ባህላዊ ሙዚቃዎች ካነሷቸው የአማራ ህዝብ በደል እና ለፍትህና ለአንድነት ካላቸው ሚና አንጻር ተተንትነዋል፡፡ በጥናቱ ውጤት መሰረትም መንግስት በሰሜን ኢትዮጵያ የህግ ማስከበር ዘመቻ ካወጀ ጀምሮ የመጀመሪያው ምዕራፍ ተጠናቀቀ እስካለበት (ከጥር 2013- ህዳር 2014 ዓ.ም) የወጡ የአማርኛ ባህላዊ ሙዚቃዎች ትኩረት አድርገው ካነሷቸው ይዘቶች መካከል ዋነኞቹ የአማራ ህዝብ በደል፣ ፍትህና የአማራ አንድነት ናቸው፡፡ በዚህም ባህላዊ ሙዚቃዎቹ የህዝብ በደልን ካላቸው ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ስነልቦናዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖዎች አንጻር በማንሳት የአማራ ህዝብ በራሱ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ስነልቦናዊና ኢኮኖሚያዊ ፍትህን ለማረጋገጥ እንዲነሳ ደጋግመው መቀስቀሳቸው ተረጋግጧል፡፡ በተጨማሪም የአንድነት መሰረቶችን (መልከዓምድራዊ አንድነት፣ የጋራ ታሪክና የጋራ ባህል) ደጋግመው በማንሳት በህብረተሰቡ ውስጥ ተቀዛቅዞ የቆየውን የአንድነት ስሜት መቀስቀሳቸው ተረጋግጧል፡፡ በተጨማሪም ባህላዊ ሙዚቃዎቹ ምንም እንኳ የተለያዩ የሀገሪቱን አካባቢዎች እየጠሩ ስለአንድነቷ ቢሰብኩም በወቅቱ ከተፈጠረው ችግር አንጻር የአማራ ህዝብ በደልና ፍትህን በማንሳት የክልል አንድነት ላይ ትኩረት ማድረጋቸው በጥናቱ ተመልክቷል፡፡ በመጨረሻም ባህላዊ ሙዚቃዎችን በጥልቀት አጥንቶና ተንትኖ ለማስተማሪያነት ማዋል ሀገራዊና ክልላዊ አንድነትን ለማስጠበቅ ግንዛቤና ተነሳሽነትን ከመፍጠር አንጻር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው በጥናቱ ይሁንታ ላይ ተመልክቷል፡፡